ደብረ ታቦር በግእዝ ቋንቋ ሲሆን የታቦር ተራራ ማለት ነው፡፡ (ማቴ 7÷1-8) የታቦር ተራራ የሚገኘው አሁን ፍልስጥኤም ተብሎ በሚጠራው ሀገር ነው፡፡ ደብረ ታቦር ወይንም የታቦር ተራራ ጌታችን አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሦስት ደቀመዛሙርቱን ይዞ ወደ ተራራው የወጣበትና ፊቱ እንደፀሐይ የበራበት ልብሱም እንደብርሃን ነጭ የሆነበት ቦታ ነው፡፡
ቤተ ክርስቲያናችን ከሚከበሩት ከዘጠኙ ዓበይት በዓላት አንዱ ደብረ ታቦር ነው፡፡ በዓሉ በየዓመቱ ነሐሴ 13 ቀን
በድምቀት ይከበራል፡፡ ታቦር ከገሊላ ባሕር በምእራባዊ ደቡብ በኩል 10ኪ.ሜ ርቆ የሚገኝ ተራራ ነው፡፡ ይህ ተራራ ከባሕር ጠለል 572 ሜትር ከፍታ አለው፡፡ «ባርቅ የተባለው ጦረኛ ሕዝበ እስራኤልን ይዞ በመዝመት ሲራ የተባለውን የሕዝብ ጠላት በታቦር ድል ነስቶ አሸንፏል» (መሳፍንት.4፡6-14)፡፡

ልበ አምላክ ቅዱስ ዳዊትም ታቦርና አርሞንኤም በስምህ ደስ ይላቸዋል፡፡ ክንድህ ከኃይል ጋር ነው ሲል በመዝሙር 88፡12 ስለ ታቦር ተራራ ዘምሯል፡፡ የታቦር ተራራ በገሊላ ከሚገኙ ተራራዎች አንደኛው ሲሆን በዛብሎን ክፍል ውስጥ ለሚኖሩ ልጆች የተሰጠ ቦታ ነው፡፡ 1ኛ ዜና.6፡77 ሐዲስ ኪዳን ግን ረጅም ተራራ ከማለት በስተቀር ታቦር ብሎ ስሙን አይጠራውም፡፡ ሆኖም ክርስቶስ በዚህ ተራራ ላይ ክብሩን እንደገለጠና የዚህም ተራራ ስም ታቦር መሆኑን ሐዋርያት በሲኖዶሳቸው ገልጠዋል፡፡ ኢትዮጵያዊው ሊቅ ቅዱስ ያሬድም ይህንን ረጅም ተራራ ደብረ ታቦር እያለ በድጓው አስፋፍቶ ጽፏል፡፡
ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደዚህ ረጅም ተራራ የወጣው ብርሃነ መለኮቱን ክብሩን ለመግለጽ ነው፡፡ በዚህ ተራራ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከሙሴና ከኤልያስ ጋር ተነጋግሮአል፡፡ እነዚህም ሁለት ታላላቅ ሰዎች በበብሉይ ኪዳን ጊዜ ስለ ክርስቶስ ትንቢት የተናገሩ ስለ እግዚአብሔር መንግሥት ያስተማሩ ቅዱሳን ነቢያት ነበሩ፡፡